League Table

ማንቸስተር ዩናይትድ፣ ሊቨርፑል እና ቼልሲ ጃሮድ ቦዌንን ለማስፈረም ፉክክር ውስጥ ናቸው

ዌስትሃም ዩናይትድ ከፕሪምየር ሊጉ የመውረድ ስጋት ውስጥ መውደቁን ተከትሎ፣ ተቀናቃኝ ክለቦች የክለቡን ምርጥ ተጫዋቾች ለመውሰድ እየተዘጋጁ ሲሆን ቼልሲ፣ ሊቨርፑል እና ማንቸስተር ዩናይትድ በጃሮድ ቦዌን ላይ ከፍተኛ ፍላጎት አሳይተዋል። ዌስትሃም ከሊጉ የሚወርድ ከሆነ ከ100 ሚሊዮን ፓውንድ በላይ ገቢ ማሰባሰብ የሚጠበቅበት ሲሆን፣ በርካታ ታላላቅ ክለቦችም ቦዌንን ለማግኘት አይናቸውን ጥለውበታል።

ይህ እንግሊዛዊ የመስመር ተጫዋች በዚህ የውድድር ዘመን 21 ግቦችን እና ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን በማመቻቸት አስደናቂ ብቃት ያሳየ ሲሆን፣ የኑኖ እስፒሪቶ ሳንቶ ቡድን ወደ ሻምፒዮንሺፕ የሚወርድ ከሆነ ቦዌን ስለ ቀጣይ ቆይታው ውሳኔ ማሳለፍ ይኖርበታል። ቦዌን በጥር 2020 ከሀል ሲቲ ዌስትሃምን ከተቀላቀለበት ጊዜ አንስቶ ድንቅ ብቃቱን እያሳየ የሚገኝ ሲሆን፣ በክለቡ ታሪክ ውስጥም ከሚወደዱ ተጫዋቾች አንዱ ለመሆን ችሏል።

የ29 ዓመቱ ተጫዋች ዌስትሃም በ2020 የኮንፈረንስ ሊግ ፍጻሜ ፊዮሬንቲናን ሲያሸንፍ የድል ግቧን ያስቆጠረ ሲሆን፣ በመጪው አርብ እንግሊዝ ለዓለም ዋንጫ የምታሳውቀው ስብስብ ውስጥ እንደሚካተትም ተስፋ ተጥሎበታል። ቦዌን ለዌስትሃም ታማኝ ሆኖ የቆየና በለንደን ቆይታው ደስተኛ እንደሆነ ቢታመንም፣ ክለቡ ከሊጉ መውረዱ ግን ቅድሚያ የሚሰጣቸውን ጉዳዮች እንዲያጤን ሊያስገድደው ይችላል።

ሊቨርፑል የቦዌን የረጅም ጊዜ አድናቂ ሲሆን፣ የፊት መስመር አማራጮቹን ለማጠናከር ተጫዋቹን ኢላማ ሊያደርግ ይችላል። ማንቸስተር ዩናይትድ በበኩሉ ለቻምፒዮንስ ሊግ ማለፉን ተከትሎ በማጥቃት መስመሩ ላይ ተጨማሪ ጥልቀት ለመፍጠር የሚፈልግ ሲሆን፣ የቦዌን በተለያዩ ቦታዎች ላይ ተጫውቶ የመርዳት ችሎታ እንደ ትልቅ ብልጫ ይታያል። ምንም እንኳን በብዛት በቀኝ መስመር ላይ ቢሰለፍም፣ በመሃል አጥቂነትም ሆነ በግራ መስመር ላይ ሊሰለፍ እንደሚችል ዩናይትዶች ያምናሉ።

ቼልሲም ሌላኛው ተጫዋቹን የሚፈልግ ክለብ ነው። ክለቡ ወጣት ተጫዋቾችን በማስፈረም ላይ ትኩረት ቢያደርግም፣ አሁን ላይ ግን ልምድ ያላቸውን ተጫዋቾች ለመጨመር ይፈልጋል። ቦዌንን ለማስፈረም ያላቸው ፍላጎት ገና በመጀመሪያ ደረጃ ላይ ቢሆንም፣ በቀኝ መስመር ላይ ፉክክር ከመፍጠሩም በላይ ለአጥቂዎቻቸው እንደ አማራጭ ሊያገለግል ይችላል ብለው ያምናሉ።

ዌስትሃም እስከ 2030 ድረስ ኮንትራት ያለውን ቦዌንን በምን ያህል ዋጋ እንደሚሸጠው ባይታወቅም፣ በዚህ ሳምንት ክለቡ ከሊጉ መውረዱ ከተረጋገጠ ግን ተጫዋቾችን ለመሸጥ ከፍተኛ ጫና ውስጥ ይገባል። ከቦዌን በተጨማሪ በማቴየስ ፈርናንዴዝ ላይ የአርሰናል፣ ዩናይትድ እና ፒኤስጂ ፍላጎት ያለ ሲሆን፣ ሆላንዳዊው የመስመር ተጫዋች ክሪሰንሲዮ ሰመርቪልም ለሽያጭ ይቀርባል ተብሎ ይጠበቃል።

ዌስትሃም ባለፈው የፋይናንስ ዓመት 104.2 ሚሊዮን ፓውንድ ኪሳራ ያስመዘገበ ሲሆን፣ በሊጉ ቢቆይም እንኳ ተጫዋቾችን መሸጥ ግድ ይለዋል። ቶተንሃም በቀሩት ሁለት ጨዋታዎች አንድ ነጥብ ብቻ የሚያገኝ ከሆነ ዌስትሃም በይፋ ከሊጉ መውረዱ ይረጋገጣል።