ከዚህ በበለጠ ግን አርሰናልን ያስገረመውና ብዙዎችን ያነጋገረው የዎልቭስ የቲክቶክ ገጽ ባለፈው ሐሙስ ያወጣው ቪዲዮ ነው። በሁለቱ ክለቦች መካከል 2-2 ከተጠናቀቀው ጨዋታ በኋላ የወጣው ይህ የ80 ሰከንድ ቪዲዮ የአርሰናልን “የጨዋታ አያያዝ” ወይም ዎልቭስ ሊገልጸው እንደፈለገው አርሰናል የሚጠቀምባቸውን “መጥፎ ዘዴዎች” (dark arts) በከፍተኛ ሁኔታ የተቸ ነበር። የዎልቭስ የማህበራዊ ሚዲያ ቡድን ጋብርኤል ማርቲኔሊ አርሰናል 2-1 እየመራ ሳለ ውጤቱን በጣቶቹ ለደጋፊዎች ሲያሳይ፣ አርሰናል የማዕዘን ምት ለመምታት የፈጀውን ረጅም ጊዜ እና ጋብርኤል ማጋልሃስ በጭንቅላት ግጭት ምክንያት ወድቆ የነበረበትን ሁኔታ በማሾፍ አሳይተዋል። በተጨማሪም ሊአንድሮ ትሮሳርድ በ90ኛው ደቂቃ ላይ በአየር ላይ በነበረ ፍጥጫ ወድቆ በነበረበት ወቅት የዎልቭስ ደጋፊዎች “ያለማቋረጥ የሚያጭበረብረው ያው አርሰናል” (Same old Arsenal, always cheating) እያሉ ሲዘፍኑ በቪዲዮው ላይ በግልጽ ይሰማ ነበር። ዎልቭስ በመጨረሻው ደቂቃ የአቻነት ግብ ሲያስቆጥርም ቪዲዮው ይሄንኑ በሳቅና በተለያዩ ምስሎች (emojis) አጅቦታል።
በዚያው ዕለት አመሻሽ ላይ ማንቸስተር ሲቲም በኤክስ (X) ገጹ ላይ ኤርሊንግ ሃላንድ እና ጃክ ግሪሊሽ ከሦስት ዓመት በፊት ከኒውካስል ጋር በነበራቸው ጨዋታ ማብቂያ ላይ ኳስ በመቆጣጠር ጊዜ ሲያባክኑ የሚያሳይ ቪዲዮ በማጋራት አርሰናልን ተሳልቆባቸዋል። አርሰናል አሁን ለፕሪሚየር ሊጉ ዋንጫ በሚያደርገው ትግል ውስጥ ትልልቅም ሆኑ ትናንሽ ተቃዋሚዎቹ በስሜቱ ላይ ለመጫወትና ለየት ያለ ስም ለመስጠት ጥረት እያደረጉ ይገኛሉ። የዎልቭስ የቲክቶክ ቪዲዮ ግን ስለ ትሮሳርድ አንድ ትልቅ እውነታ ዘንግቷል። በ73ኛው ደቂቃ ላይ ተቀይሮ የገባው ትሮሳርድ፣ ቀደም ብሎ ቢጫ ካርድ በነበረው ሳንቲያጎ ቡዌኖ በደረሰበት ጥቃት መንጋጋው ላይ ጉዳት ደርሶበት ሜዳውን ለቆ ለመውጣት ተገዶ ነበር። የአርሰናል ዶክተሮች ጊዜ ለማባከን በሴራ ተባባሪ ተደርገው መቆጠራቸው አግባብ ባይሆንም፣ ቪዲዮው ግን በማህበራዊ ሚዲያ ላይ በሰፊው በመሰራጨቱ ብዙዎች እውነታውን ለመመልከት አልፈለጉም።
አርሰናል ከዎልቭሱ ጨዋታ በኋላ ቶተንሃምን ለማሸነፍ ይገባው ነበር፤ አሸንፏልም። ነገር ግን በ53ኛው ደቂቃ ላይ አርሰናል 2-1 እየመራ ሳለ ራንዳል ኮሎ ሙአኒ በጋብርኤል ላይ መጠነኛ ግፊት አድርጓል ተብሎ ግቡ ሳይጸድቅ መቅረቱ አነጋጋሪ ነበር። ጋብርኤል ባለፈው መስከረም በኒውካስል ጨዋታ ላይ ከኒክ ዎልቴሜድ ጋር ተመሳሳይ ሁኔታ ገጥሞት ዳኛው ጥፋት አይደለም በማለታቸው ግብ ተቆጥሮባቸው ነበር። በዚህኛው ጨዋታ ግን ውሳኔው ለእርሱ ተሰጥቷል። ጋብርኤል ከጨዋታው በኋላ ዝም ከማለት ይልቅ አራት ካርዶችን የያዘ ምስል በማህበራዊ ሚዲያ በማጋራት የቶተንሃሙን ሪቻርሊሰንን ጭምር መጥቀሱ (tag ማድረጉ) በምላሹ ብዙ የመሳለቂያ ምስሎች እንዲወርዱበት አድርጓል።
ሚኬል አርቴታ ለዚህ “የውጭ ጩኸት” የሰጠው ምላሽ በትኩረት መስራትና የተጫዋቾቹን መንፈስ ማጠናከር ነው። ፔፕ ጋርዲዮላ አርሰናልን “በአለም ላይ ምርጡ ቡድን” ሲል ገልጾታል። የዎልቭስ አሰልጣኝ ሮብ ኤድዋርድስም አርሰናል በሊጉ ምርጡ ቡድን መሆኑን ለአርቴታ በግል መልዕክት ገልጿል። አርሰናል ኳስን ለመቆጣጠርና ተቃዋሚ ላይ ጫና ለመፍጠር የሚያደርገው ጥረት በብዙ አሰልጣኞች ዘንድ አድናቆት አትርፏል። በኦፕታ (Opta) መረጃ መሰረት አርሰናል በዚህ የውድድር ዘመን ጊዜ በማባከን ሰባት ቢጫ ካርዶችን የተመለከተ ሲሆን፣ ይህም ከቼልሲ ጋር እኩል ነው፤ እንደ ቦርንመዝ እና ፉልሃም ካሉ ክለቦችም ያነሰ ነው። ጨዋታን ዳግም ለማስጀመር በሚወስዱት ጊዜም አርሰናል ከሰንደርላንድ፣ ብሬንትፎርድ እና ክሪስታል ፓላስ ዝቅ ብሎ በሰባተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። አርቴታና ተጫዋቾቹ አሁንም በማዕበል ውስጥ ናቸው፤ ቼልሲም ሌላ ፈተና ይዞ ይጠብቃቸዋል። አርሰናል ጽናቱን ጠብቆ ከቀጠለ ዋንጫውን በከባድ ትግል እንደሚያገኘው ጥርጥር የለውም።