ሊቨርፑል 4 ለ 0 ባሸነፈበት በዚህ ጨዋታ፣ ሳላህ የመጨረሻውን ግብ ያስቆጠረበት መንገድ እጅግ ማራኪ ነበር። ኳሷን በቀኝ በኩል ይዞ ከፍሎሪያን ዊርትዝ ጋር በመቀባበል፣ በግራ እግሩ አጥፎ ወደ ግቡ የላካት ኳስ መረቡ ላይ እስክትረፍርፍ ድረስ በአንፊልድ አየር ላይ ስትንሳፈፍ የታየችው ውበት ልዩ ነበር። ግቡን ካስቆጠረ በኋላም ሳላህ ደስታውን ለደጋፊዎቹ በመግለጽ ሜዳውን ስሟል። ይህም የሳላህ የንግስና ምሽት ይመስል ነበር፤ ሆኖም ምሽቱ የመጨረሻዎቹን ጊዜያት የመሰናበቻ ትዝታም ያዘለ ይመስላል። ከክረምቱ በፊት ቢያንስ አንድ ተጨማሪ የሻምፒዮንስ ሊግ ጨዋታ ከፓሪስ ሳን ዠርሜን ጋር እዚህ ይኖራል፤ ነገር ግን እንደዛሬው ያለ ድባብ ይኖረው እንደሆነ እርግጠኛ መሆን አይቻልም።
የአርኔ ስሎት ቡድን በመጀመሪያው አጋማሽ በጋላታሳራይ ግብ ላይ ተደጋጋሚ ጫና ቢያሳድርም ውጤታማ አልነበረም። ሊቨርፑል 15 ሙከራዎችን አድርጎ አንድ ግብ ብቻ ነው ያስቆጠረው። ጨዋታው በመጀመሪያው አጋማሽ ልክ እንደ ሰካራሞች ድብድብ ግራ የተጋባና ስርአት አልባ ይመስል ነበር። በዚያ መሃል ሳላህም ቢሆን መጥፎ የሚባል ጊዜ እያሳለፈ ነበር። ገና በ20ኛው ደቂቃ ላይ ያገኘውን ግልጽ የጎል አጋጣሚ ስቶታል። በወቅቱ ሳላህ ጨዋታው በዙሪያው ሲከናወን ዝም ብሎ የሚመለከት እንጂ ተሳታፊ አይመስልም ነበር።
ዶሚኒክ ሶቦስላይ ከመዓዘን ምት የተላከለትን ኳስ ወደ ግብ በመለወጥ ሊቨርፑልን ቀዳሚ አደረገ። በመጀመሪያው አጋማሽ ማጠናቀቂያ ላይ ሊቨርፑል የፍጹም ቅጣት ምት አግኝቶ ሳላህ ቢመታውም፣ ኳሷ ደካማ በመሆኗ በረኛው ኡጉርካን ቻኪር በቀላሉ ሊያድንበት ችሏል። በወቅቱ ጨዋታው በአርኔ ስሎት ላይ ከባድ ሊሆን እንደሚችል ተሰግቶ ነበር። የአንፊልድ ደጋፊዎች ጉልበት የሚታወቅ ቢሆንም፣ ስሎት ግን ከደጋፊው ጋር ያለው ግንኙነት እንደ የርገን ክሎፕ አልሆነም። ክሎፕ ሽንፈትን እንኳ ክብር ባለው መንገድ እንዲቀበሉ የማድረግ ችሎታ ነበራቸው።
ጋላታሳራይ ጨዋታውን ለማዘግየት ጥረት አድርጓል። ተጫዋቾች በወደቁ ቁጥር የህክምና ባለሙያዎች በዝግታ ወደ ሜዳ እየገቡ ጊዜ ሲያባክኑ የአሰልጣኝ ስሎትን ንዴት ቀስቅሰዋል። ስሎት በሜዳው ዳር ሆኖ በንዴት ስሜቱን ሲገልጽና ከዳኞች ጋር ሲከራከር ታይቷል።
ከእረፍት በኋላ ግን ሳላህ ተቀይሮ መጣና ጨዋታውን ለወጠው። መጀመሪያ ለሁጎ ኤኪቲኬ ድንቅ ኳስ አመቻችቶ በማቀበል ሁለተኛ ግብ እንዲቆጠር አደረገ። በመቀጠልም የእሱ ጠንካራ ምት በሪያን ግራቨንበርች አማካኝነት ሶስተኛ ግብ ሆነ። ሳላህ ጥቂት የጉዳት ስሜት ታይቶበት በደጋፊዎች ሞቅ ያለ ጭብጨባ ታጅቦ ከሜዳ ሲወጣ፣ ምሽቱ ለሳላህ እንደ ክብር መግለጫ ሆኖ አልፏል። ሳላህ ባለፈው የውድድር ዘመን የሊግ ዋንጫ ስኬት ላይ ከማንም በላይ ትልቅ ድርሻ እንደነበረውና ለአሰልጣኙም ተጨማሪ እፎይታ የሰጠበት ምሽት ሆኗል።