በዚህ ወር አርሰናል ብራይተንን ባሸነፈበት ጨዋታ ፒዬሮ ሂንካፒዬ መሬት ላይ ወድቆ በጭንቅላቱ ኳስ ሲከላከል የታየ ሲሆን፣ ጋብርኤል ደግሞ ካርሎስ ባሌባ የሞከራትን ኳስ ከግብ መስመር ላይ ማውጣትን ጨምሮ 14 ግልጽ ኳሶችን አርቆ ነበር። ሚኬል አርቴታ በተደጋጋሚ እንደሚናገረው፣ አርሰናል ሌቨርኩሰንን ባሸነፈበት ጨዋታ ለ25ኛ ጊዜ መረቡን ሳያስደፍር ሲወጣ ቁጥር 6ቱ ተከላካይ ለቡድኑ “መነሳሳትን የሚፈጥር” ተጫዋች ነው። ጋብርኤል በዚህ የውድድር ዘመን 38 ኳሶችን በመከላከል የቡድኑን 29 በመቶ ድርሻ የያዘ ሲሆን፣ እሁድ በካራባኦ ካፕ ፍፃሜ ማንቸስተር ሲቲን ለሚገጥመው የአርሰናል መከላከያ የማይተካ መሪ ነው። “እኔ ተከላካይ ነኝ፣ ስለዚህ ይህን ጉልበት ለቡድን አጋሮቼ እና ለደጋፊዎቻችን ማምጣት አለብኝ” ይላል ጋብርኤል:: “ሜዳ ላይ ስሆን ሁሉንም ነገር እሰጣለሁ። ሁሉንም ሰው ለማነቃቃት እሞክራለሁ። ትልቅ ፍልሚያ እንደሚሆን አውቃለሁ፣ ለዚህም ዝግጁ ነኝ።”
ሁሉም አይኖች በጋብርኤል እና በኧርሊንግ ሀላንድ ፍጥጫ ላይ ያርፋሉ፤ ሁለቱም ይህን ፉክክር እንደሚወዱት መናገራቸው ደግሞ አያስደንቅም። “ይህ ደስ የሚል ነገር ነው – እንደሰትበታለን” ይላል ጋብርኤል:: “እውነቱን ለመናገር እያንዳንዱን ጨዋታ እና እያንዳንዱን አጥቂ እወዳለሁ። ስራዬ በመሆኑ መታገል ደስ ይለኛል። እሱ ምርጥ ተጫዋች ነው፣ እኔንም መጋፈጥ እንደሚወድ አስባለሁ። በዚህ ሊግ መጫወት ቀላል አይደለም፤ ጠንካራ መሆን እና እያንዳንዱን ፍልሚያ ማሸነፍ ይጠይቃል።” አርሰናል እ.ኤ.አ. በ2023 የዋንጫ ተስፋውን ካጨለመው የ4-1 ሽንፈት በኋላ በስድስት ጨዋታዎች በሲቲ አልተሸነፈም። ምንም እንኳን ሀላንድ በሴፕቴምበር ወር በኤምሬትስ 1-1 በተጠናቀቀው ጨዋታ ግብ ቢያስቆጥርም፣ አርሰናል ግን ውጤቱን ማስጠበቅ ችሏል። ጋብርኤል እ.ኤ.አ. በ2020 አርሰናል ኤፍኤ ካፕን ካነሳ ከጥቂት ወራት በኋላ ከሊል የተቀላቀለ ቢሆንም፣ እስካሁን ትልቅ ዋንጫ አላሸነፈም። ሆኖም ለዚህ ቅዳሜና እሁድ “ጥሩ ስሜት” አለው። “ለዚህ ጨዋታ በጣም ጓጉተናል” ይላል። “ካለፈው ብዙ ተምረናል፤ ሁሉንም ጨዋታ ማሸነፍ እንፈልጋለን፣ ነገር ግን ፕሪሚየር ሊግ ከባድ እንደሆነ እናውቃለን። ባለፉት ሶስት አመታት ዋንጫውን አላገኘንም፣ ዘንድሮ ግን በጥሩ ሁኔታ ጀምረናል። የተቻለንን ሁሉ እናደርጋለን፤ አሁን ባለነበት ጥሩ ሁኔታ ቀጥለን መጨረሻው ምን እንደሚሆን እናያለን።”
ማርቲን ኦዴጋርድ ጋብርኤል የማርሻል አርት (MMA) ተዋጊ ሊሆን ይችል ነበር ሲል፣ ቡካዮ ሳካ ደግሞ ብራዚላዊው ያለው አካላዊ ጥንካሬ ለጥበቃ ሰራተኛነት እንደሚመቸው በቀልድ ይናገራሉ። ጋብርኤልም በዚህ እየሳቀ “እነሱ ያውቁኛል፣ በየቀኑ አብረን ነው የምንለማመደው። ምናልባት ከእግር ኳስ በኋላ የጥበቃ ሰራተኛ እሆን ይሆናል?” ብሏል። ጋብርኤል በታዳጊነቱ በብራዚል ሁለተኛ ዲቪዚዮን አቫይ ለተባለ ክለብ ሲጫወት ነበር በሊል አይን ውስጥ የገባው። በወጣትነቱ በጣም “ጨካኝ” ተከላካይ እንደነበር ይናገራል፦ “ከጓደኞቼ ጋር ስጫወት ‘ኧረ ተረጋጋ አንተ ፕሮፌሽናል ነህ’ ይሉኝ ነበር። እኔ ግን ሁልጊዜም እንደማደርገው ነው። እግር ኳስ ስንጫወት ወደ አንተ ስመጣ በአእምሮዬ ያለው ቤቴን መከላከል ነው። ለእኔ ቆንጆ እግር ኳስ ማለት የሚያምር ቅብብል ብቻ ሳይሆን፣ የምትከላከልበት መንገድም ጭምር ነው።”
ጋብርኤል በጃንዋሪ ወር በበርንማውዝ ላይ ግብ ሲያስቆጥር፣ 20 የፕሪሚየር ሊግ ግቦችን ያስቆጠረ ሁለተኛው የአርሰናል ተከላካይ መሆን ችሏል። እ.ኤ.አ. በ2020 ወደ ሊጉ ከመጣ በኋላ በቦታው ላይ ከሚጫወቱ ተጫዋቾች ሁሉ በሰባት ግቦች ብልጫ አለው። በበርንማውዙ ጨዋታ ስህተት ሰርቶ ኢቫኒልሰን ግብ እንዲያስቆጥር ቢፈቅድም፣ ከአምስት ደቂቃ በኋላ ግን አቻነቷን ግብ ማስቆጠሩ የእድገቱ ማሳያ እንደሆነ ያምናል። “ስህተት ሰርተህ ግብ ሲቆጠርብህ ቀላል አይደለም፤ ነገር ግን በጨዋታው ውስጥ መረጋጋት አለብህ። ከአራት አመት በፊት ከነበረኝ አስተሳሰብ አሁን ተቀይሯል፣ ብዙ ተምሬያለሁ። እንደ ተከላካይ መረጋጋት እና በድጋሚ መነሳት እንዳለብኝ አውቃለሁ።”