League Table

ኤቨርተን ለሂልስቦሮ ሰለባዎች በሂል ዲኪንሰን ስታዲየም መታሰቢያ አቆመ

ኤቨርተን የሂልስቦሮ አደጋ 37ኛ ዓመት መታሰቢያን በማስመልከት፣ በህገ-ወጥ መንገድ ህይወታቸው ለለፈው 97 የሊቨርፑል ደጋፊዎች በሂል ዲኪንሰን ስታዲየም ቋሚ መታሰቢያ አቁሟል። ረቡዕ እለት በኤቨርተን አዲሱ ስታዲየም በተካሄደው የክብር ስነ-ስርዓት ላይ የሂልስቦሮ ቤተሰቦች ተወካዮች እና የሊቨርፑል እግር ኳስ ክለብ ተወካዮች ተጋብዘው ለ97ቱ ሰለባዎች ክብራቸውን የገለጹ ሲሆን፣ ከደቡብ ስታንድ (South Stand) ውጭ የተሰራውን የመታሰቢያ ታብሌትም መርቀዋል።

እ.ኤ.አ. በ1989 በኤፍኤ ካፕ የግማሽ ፍፃሜ ጨዋታ አደጋው በሚከሰትበት ወቅት የሊቨርፑል አሰልጣኝ የነበሩት ሰር ኬኒ ዳልግሊሽ እና የቀድሞው ኮከብ ኢያን ረሽ በክለቡ ስም የአበባ ጉንጉን አኑረዋል። በሂልስቦሮ አደጋ ታላቅ ወንድማቸውን ማይክልን ያጡት እና የታወቁ የሂልስቦሮ ተሟጋች እንዲሁም የኤቨርተን ደጋፊ የሆኑት ስቲቨን ኬሊ፣ በመታሰቢያው ላይ የአበባ ጉንጉን ካኖሩት መካከል አንዱ ነበሩ። በስነ-ስርዓቱ ላይ የኤቨርተን ታዋቂ ተጫዋች ግሬም ሻርፕ፣ የክለቡ አምባሳደሮች ኢያን ስኖዲን እና ግርሃም ስቱዋርት፣ እንዲሁም የክለቡ ዋና ስራ አስፈፃሚ አንገስ ኪኔር እና የሊቨርፑል አቻቸው ቢሊ ሆጋን ተገኝተዋል።

ሁለቱ የአካባቢው ተቀናቃኞች እሁድ እለት በሂል ዲኪንሰን ስታዲየም ለመጀመሪያ ጊዜ በሚካሄደው የመርሲሳይድ ደርቢ ጨዋታ ይገናኛሉ። የሊቨርፑል ተጫዋቾች፣ ሰራተኞች እና ዋና አሰልጣኙ አርኔ ስሎት ረቡዕ እለት በክለቡ የልምምድ ሜዳ በሚገኘው የሂልስቦሮ መታሰቢያ አጠገብ የዝምታ ጊዜ አሳልፈዋል። መላው ክለብ እ.ኤ.አ. ኤፕሪል 15 ቀን 1989 ከኖቲንግሃም ፎረስት ጋር የተደረገው ጨዋታ በተቋረጠበት ሰዓት 3:06 ላይ የዝምታ ጊዜ የዘከረ ሲሆን፣ በኋላም በአንፊልድ ስታዲየም መሃል ሜዳ 97 ፊኛዎች ወደ አየር ተለቀዋል።