ባለፈው ወር ሊያም ሮዜኒየርን ከስንብት በኋላ ካለም ማክፋርሌንን እስከ የውድድር ዘመኑ መጨረሻ ድረስ በጊዜያዊ አሰልጣኝነት የሾመው ቼልሲ፣ የፉልሃሙን ማርኮ ሲልቫን፣ የክሪስታል ፓላሱን ኦሊቪየር ግላስነርን እና የቀድሞውን የፍላሜንጎ አሰልጣኝ ፊሊፔ ሉዊስን በእጩነት ተመልክቷል። ሲልቫ በውድድር ዘመኑ መጨረሻ ውሉ የሚጠናቀቅ ሲሆን ግላስነር ደግሞ ከኮንፈረንስ ሊግ ፍፃሜ በኋላ ፓላስን እንደሚለቁ ታውቋል። የስታምፎርድ ብሪጅ የበላይ ኃላፊዎች የሚፈልጉትን አሰልጣኝ ለማግኘት እንደሚችሉ እምነት ያላቸው ሲሆን ከአሎንሶ ወኪሎች ጋር የተደረገው የመጀመሪያ ደረጃ ንግግርም በተስፋ ተሞልቷል።
በ2024 ከባየር ሌቨርኩሰን ጋር ቡንደስሊጋውን በማሸነፍ በአውሮፓ ውስጥ ካሉ ምርጥ ወጣት አሰልጣኞች አንዱ መሆኑን ያስመሰከረው የ44 ዓመቱ አሎንሶ፣ በዚህ የውድድር ዘመን መጀመሪያ ላይ ሪያል ማድሪድን ከለቀቀ በኋላ ስራ ፈትቶ ቆይቷል። ቼልሲም አሎንሶን ቢያንስ ላለፉት ሶስት ዓመታት በክትትል ውስጥ አቆይቶታል። በአሎንሶ የጨዋታ ፍልስፍና እና ዘይቤ ለቼልሲ ወጣት ስብስብ ተስማሚ ነው የሚል እምነት በክለቡ ውስጥ አለ። የቀድሞው የስፔን ብሄራዊ ቡድን አማካይ በእግር ኳስ ዓለም ያለው ዝና የተጫዋቾቹን ክፍል ለመቆጣጠር እና ታዋቂ ተጫዋቾችን ወደ ክለቡ ለመሳብ እንደሚረዳም ይታመናል።
አሎንሶ አሁን ወደ እንግሊዝ ለመምጣት ይወስናል ወይስ እረፍት መውሰድን ይመርጣል የሚለው ገና አልታወቀም። የሊቨርፑል ስራ ክፍት እስኪሆን እየጠበቀ ነው የሚሉ ወሬዎች ግን ውድቅ ተደርገዋል። በአሁኑ ወቅት የመርሲሳይዱ ክለብ በዚህ ክረምት ከአርኔ ስሎት ጋር እንደሚቀጥል ቢታመንም እስካሁን በይፋ አልተረጋገጠም። አሎንሶ ከ2004 እስከ 2009 በሊቨርፑል ተጫውቶ በ2005 የሻምፒዮንስ ሊግን እንዲሁም በሚቀጥለው ዓመት የኤፍኤ ካፕን በማሸነፉ በደጋፊዎች ዘንድ ትልቅ ክብር አለው።
ቼልሲ ኤንዞ ማሬስካን ተክቶ ለሶስት ወር ከግማሽ ብቻ የቆየውን ሮዜኒየርን ካሰናበተ በኋላ “ራስን የመገምገም” ጊዜ ውስጥ ገብቷል። በክለቡ የተጫዋቾች ምልመላ ክፍል በኩል የታመነበት ጉዳይ ቡድኑ ይበልጥ በአካላዊ ብቃት ጠንካራ መሆን እንዳለበት ነው። ይህ ደግሞ የበርንማውዝ ቡድናቸው በፕሪምየር ሊጉ ከፍተኛ ጫና ከሚፈጥሩት ውስጥ አንዱ የሆነውን የኢራኦላን ተመራጭነት ከፍ ያደርገዋል። ቼልሲ ስለ ስራው ለማነጋገር ከኢራኦላ ጋር ተገናኝቷል። ስፔናዊው አሰልጣኝ በበርንማውዝ ለሰሩት ስራ ትልቅ አክብሮት ያለ ሲሆን ትልቅ ክለብ የመምራት ብቃት እንዳላቸውም ይታመናል።
ኢራኦላ ባለፈው አንድ ዓመት ውስጥ በመከላከያ እና በማጥቃት መስመር ላይ በርካታ ቁልፍ ተጫዋቾችን ቢያጡም ቡድኑን ለሻምፒዮንስ ሊግ ማጣሪያ ተፎካካሪ በማድረግ ምላሽ ሰጥተዋል። የደቡብ ዳርቻው ክለብ የውድድር ዘመኑ ሊጠናቀቅ ሁለት ጨዋታዎች እየቀሩት ከአምስተኛ ደረጃ በአራት ነጥቦች ብቻ ርቆ ይገኛል። ኢራኦላ ከማንቸስተር ዩናይትድ ጋርም እንደተገናኙ ቢታወቅም ዩናይትዶች ግን ከማይክል ካሪክ ጋር የመቀጠል ፍላጎት እንዳላቸው ፍንጮች አሉ። በአሁኑ ወቅት በርንማውዝ አሳዛኝ የውድድር ዘመኑን የአውሮፓ ውድድሮች ተሳትፎን በመንጠቅ ለመታደግ ከሚሞክረው ቼልሲ በስድስት ነጥቦች በልጦ ይገኛል። ቼልሲ ቅዳሜ በኤፍኤ ካፕ ፍፃሜ ከማንቸስተር ሲቲ ጋር ሲጋጠም ማክፋርሌን ቡድኑን በቴክኒክ ቀጠናው ሆነው ይመራሉ።