ቡድኑ ካሳየው ደካማ አፈጻጸም በኋላ፣ እሁድ ከሊድስ ጋር ለሚደረገው የኤፍኤ ካፕ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ድረስ በአሰልጣኝነት መንበራቸው ላይ ስለመቆየታቸው ጥያቄዎች መነሳታቸው አይቀርም። ቼልሲ ምንም ግብ ሳይያስቆጥር በተከታታይ አምስተኛውን የሊግ ሽንፈት ካስተናገደ በኋላ ሮሴኒየር ሲናገሩ፦ “ይህ በሁሉም የጨዋታው ገፅታዎች ተቀባይነት የሌለው ነበር። በአመለካከት ረገድም ተቀባይነት የለውም። ሁልጊዜ እየወጣሁ ተጫዋቾቹን እከላከላለሁ፣ የዛሬው ግን ተቀባይነት የሌለው ነው” ብለዋል።
“አሁን ላይ የሆነ ነገር በአስቸኳይ መቀየር አለበት። ራሳችንን በመስተዋት ማየት ይኖርብናል። እያየናቸው ያሉትን አንዳንድ ነገሮች እየመጣሁ መከላከል አልችልም። አጠቃላይ አመለካከት፣ መንፈስ እና ቆራጥነት ጎድሎ ነበር፤ ምናልባትም ከ11ዱ ተጫዋቾች መካከል ሶስቱ ወይም አራቱ ብቻ ናቸው ጥረት ያደረጉት፣ ይህም ለዚህ ክለብ በቂ አይደለም። መጥቼ መዋሸት አልችልም፣ ይህ ለዚህ ክለብ የማይመጥን አፈጻጸም ነበር” ሲሉ አክለዋል።
ኮል ፓልመርን ባላሰለፈው እና ባልተለመደ የ 3-5-2 አሰላለፍ ወደ ሜዳ በገባው የቼልሲ ቡድን ላይ ፈርዲ ካዲዮግሉ፣ ጃክ ሂንሸልዉድ እና ዳኒ ዌልቤክ ያስቆጠሯቸው ግቦች ለብራይተን ድልን አስገኝተዋል።
የሮሴኒየር የጨዋታው ትንተና ጠንከር ያለ ነበር፦ “ከሚጠበቀው ደረጃ በጣም የራቀ ነበር፤ ታክቲክ ብቻ ሳይሆን ኳስ ለመንጠቅ የሚደረጉ ጥረቶች፣ ግጥሚያዎች፣ ጥንካሬ፣ መንፈስ፣ ጉልበት እና ፍላጎት ሁሉም ጎድለው ነበር፤ ለሽንፈታችንም ምክንያት የሆነው ይሄው ነው። ደንዝዣለሁ፤ በጣም ተቆጥቻለሁ። ሁልጊዜ የማየውን ነው የምናገረው፣ ያ ደግሞ ተቀባይነት የሌለው ነበር። ያስተናገድናቸው ግቦች ተቀባይነት የሌላቸው ናቸው፣ ለዚህም እጄን መስጠት አለብኝ።”
የቀድሞው የብራይተን ተጫዋች እና አሰልጣኝ አክለውም፦ “ከሙያዊ ብቃት አንጻር አፈጻጸሙ አልነበረም። በእውነት በጣም አስቸጋሪ ምሽት ነው። በዚህ ድንቅ ክለብ ውስጥ በቆየሁበት ጊዜ ያጋጠመኝ ከሁሉ የከፋ ምሽት ነው። ዛሬ የታዘብኳቸውን አንዳንድ ነገሮች ዳግመኛ ማየት አልፈልግም” ብለዋል።
ብራይተን እንግዳውን ቼልሲን በመቅደም ወደ ስድስተኛ ደረጃ ከፍ ብሏል፤ ይህም ለቀጣዩ የውድድር ዘመን በአውሮፓ መድረክ ለመሳተፍ የሚያደርገውን ጉዞ አቃርቦለታል። የአሰልጣኙ ፋቢያን ሁርዘለር ስለደረጃቸው መሻሻል ሲናገሩ፦ “ለእኛ ያን ያህል አስፈላጊ አይደለም። ትኩረታችንን በአፈጻጸማችን እና በትክክል መስራት በሚገባን ነገሮች ላይ ማድረግ አለብን። ከራሳችን ከፍተኛ ግምት አለን” ብለዋል።