ፕሪምየር ሊጉ ሰኞ ዕለት ባወጣው መግለጫ ቼልሲ በአብራሞቪች ዘመን ለሰባት ዓመታት ያህል ተጫዋቾችን ለማስፈረም 47.5 ሚሊዮን ፓውንድ የሚጠጋ ህገ-ወጥ ክፍያዎችን “በማጭበርበር እና በመደበቅ” በመፈጸሙ የ10.75 ሚሊዮን ፓውንድ የገንዘብ ቅጣት፣ የታገደ የዝውውር እገዳ እና የዘጠኝ ወራት የአካዳሚ ተጫዋቾች ዝውውር እገዳ ተጥሎበታል። በቅጣት ስምምነቱ ላይ እንደተገለጸው፣ ቼልሲ የPSR ደንቦችን አልጣሰም ተብሏል። በተጨማሪም የሊጉ የበላይ አካል የክለቡ አዲሶቹ ባለቤቶች ክሊርሌክ ካፒታል ጥሰቶቹን በራሳቸው ፍቃድ ለሊጉ በማሳወቃቸው አድናቆት ችሯቸዋል። የፕሪምየር ሊጉ ዋና ስራ አስፈጻሚ ሪቻርድ ማስተርስ በፈረሙበት ስምምነት መሰረት፣ በዚህ ጉዳይ ላይ የነጥብ ቅጣት መጣል “ተገቢ አልነበረም” ብለዋል።
በኤቨርተን በኩል የፕሪምየር ሊጉ የዲሲፕሊን ስርዓት ሁለት አይነት ሚዛን ይጠቀማል በሚል ከፍተኛ ቁጣና ቅሬታ ተፈጥሯል። ኤቨርተን የፋይናንስ ደንብ ጥሶ የነጥብ ቅጣት በተጣለበት ወቅት የዌስትሃም አሰልጣኝ የነበሩት ሞዬስ፣ ሊጉ ለቼልሲ ቅጣት የሰጠው ማብራሪያ ለትችት የሚዳርግ ነው ብለው ያምናሉ። የአሁኑ የኤቨርተን አሰልጣኝ “ስለ ጉዳዩ ትንሽ ተጨማሪ ነገር መስማት እፈልጋለሁ” ብለዋል። “ተጨማሪ ዝርዝሮችን እና ለምን እንደሆነ ማወቅ እፈልጋለሁ፤ ይህ በቼልሲ ላይ ያለኝ ጥላቻ አይደለም። ኤቨርተን ከፍተኛ የነጥብ ቅጣት ሲጣልበት እኔ እዚህ አልነበርኩም። የገንዘብ ቅጣቱ ምን እንደሆነ እና ለምን እንደተወሰነ በሚገባ ያብራሩት አይመስለኝም። ለምሳሌ ከነጥብ ቅጣት ይልቅ ለምን ወደ የገንዘብ ቅጣት እንደደረሱ ትንሽ ተጨማሪ ብንሰማ ጥሩ ይመስለኛል” ሲሉ ሀሳባቸውን ሰጥተዋል።