ጎሉ መጀመሪያ ላይ ከጨዋታ ውጪ በሚል ተሰርዞ የነበረ ቢሆንም፣ የቪዲዮ ረዳት ዳኛው (VAR) ማርቲኔዝ አማካዩን እየተቆጣጠረው ቢሆንም ፈርናንዴዝ በጨዋታው ውስጥ ጣልቃ አልገባም የሚል ውሳኔ አስተላልፏል። ይህም ካሪክን ለቅሬታ እና ግራ መጋባት ዳርጓቸዋል። የዩናይትዱ አሰልጣኝ ሲናገሩ “በወቅቱ ነገሩን ሙሉ በሙሉ አላየሁትም ነበር። ነገር ግን የተሰጠኝ ማብራሪያ ተጫዋቹ በጨዋታው ውስጥ ጣልቃ አልገባም የሚል ሲሆን፣ ይህ ደግሞ በፍጹም ሊገባኝ አልቻለም” ብለዋል።
“ዳኞችን ለመርዳት በሚል ይህን ያህል የሰው ኃይል፣ ስክሪኖች እና ቢሮዎች ተመድበው ትክክለኛ ውሳኔ ላይ ለመድረስ ለምን እንደሚቸገሩ ሊገባኝ አይችልም” ያሉት ካሪክ፣ “ከግብ ስድስት ሜትር ርቀት ላይ ሆነህ ኳሱን ለመንካት እየሞከርክ እና ሊሳንድሮ ለዛ ምላሽ እንዲሰጥ እያደረግክ በጨዋታው ውስጥ ጣልቃ አልገባህም ተብሎ ደንቡ የሚተረጎም ከሆነ፣ ጨዋታው በዳኞች እየታየበት ያለው መንገድ በእጅጉ ያሳስባል” ሲሉ አክለዋል።
ከዳኞች ማህበር (Pro Ref) ይቅርታ ቢጠየቁ ፍላጎታቸው እንደሆነ ለተጠየቁት ጥያቄ “አዎ፣ ያ በጣም ጥሩ ይሆን ነበር። በጉጉት ነው የምጠብቀው” ሲሉ በፌዝ መልክ መልሰዋል። “ለዚህ ጉዳይ ሌላ ምን ዓይነት ማብራሪያ ሊሰጥ እንደሚችል አላውቅም። ሁላችንም በጨዋታ ውስጥ ጣልቃ መግባት የሚለው ደንብ ምን ማለት እንደሆነ እናውቃለን፣ ነገሩ ደግሞ በጣም ግልጽ ነው። ከዚህ በላይ ግልጽ ሊሆን አይችልም” ብለዋል።
በሌላ በኩል የሲቲው አሰልጣኝ ኢንዞ ማሬስካ ፈርናንዴዝ በጨዋታው ውስጥ ጣልቃ እንዳልገባ በጽኑ ተከራክረዋል። “አዎ – አራተኛው ዳኛም ኤርሊንግ ከጨዋታ ውጪ እንዳልነበረ ነግሮናል” ብለዋል። በ199ኛው የማንቸስተር ደርቢ ሌላኛው አነጋጋሪ ውሳኔ በ22ኛው ደቂቃ ላይ ለፊል ፎደን የተሰጠው ቀይ ካርድ ነበር። አጥቂው የዩናይትዱን ካፒቴን ብሩኖ ፈርናንዴዝን በሆዱ ላይ የመታው ቢሆንም፣ ይህ የሆነው ግን የዩናይትዱ ካፒቴን መጀመሪያ ካረገጠው በኋላ ነበር። ማሬስካ ዳኛው ማይክል ኦሊቨር ለፎደን የሰጡትን ቀይ ካርድ ቢደግፉም፣ ብሩኖም ጭምር መሰናበት ነበረበት የሚል እምነት አላቸው። “የፊል ፎደን ቀይ ካርድ ተገቢ ነው፣ ነገር ግን ብሩኖም ቀይ ካርድ ሊሰጠው ይገባ ነበር ብዬ አስባለሁ። ድርጊቱን በድጋሚ ስንመለከተው የፊል ድርጊት የተቃውሞ ምላሽ በመሆኑ ግልጽ ቀይ ካርድ ነው፣ ነገር ግን የብሩኖንም ድርጊት ማየት ይቻላል” ብለዋል።
ሲቲ በአሁኑ ወቅት በ12 ነጥብ በግብ ልዩነት ከአርሰናል ቀጥሎ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጥ፣ ዩናይትድ በ4 ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ካሪክ ግን “የምንፈልገው ደረጃ ላይ እንደምንደርስ እርግጠኛ ነኝ” ብለዋል። “እስካሁን የፈለግነውን ያህል እና ሊኖረን ይገባ የነበረውን ያህል ነጥብ አላገኘንም። ይህን አምነን መቀበል አለብን። ይህም ወደፊት የምናደርገውን ጉዞ እና ለውድድር ዘመኑ ያለንን ተስፋ እንዲሁም እንደ ቡድን ልናሳካው የምንችለውን ነገር አይቀይረውም። ባለፉት ጊዜያት ጥሩ መሻሻሎችን አሳይተናል፣ ይህንም አጠናክረን እንቀጥላለን” ሲሉ ንግግራቸውን አጠቃልለዋል።