FSG በበኩሉ ዓርብ ዕለት በሰጠው መግለጫ፣ ከ1892 ጋር የተደረገው ስምምነት እ.ኤ.አ. በ2010 በ300 ሚሊዮን ፓውንድ ከገዛው ክለብ ለመውጣት የታለመ ስትራቴጂ አካል እንዳልሆነና ወደፊት ተጨማሪ ድርሻዎችን ለጥምረቱ ለመሸጥ እንደማይገደድ አጽንኦት ሰጥቷል። አሁንም ሁኔታው ያ ቢሆንም፣ FSG በሚቀጥሉት 12 ወራት ውስጥ ድርሻውን ለመሸጥ ወይም ለመቀነስ ከወሰነ፣ 1892 ሆልዲንግስ የክለቡን የአብላጫ ድርሻ የመግዛት አማራጭ የሚሰጥ ስምምነት አለው። የሊቨርፑል ዋና ባለቤት (FSG) ይህ ለ1892 የተሰጠው አማራጭ በሚቀጥሉት 12 ወራት ውስጥ ተግባራዊ ሊሆን የሚችልና ወደ ተጨማሪ ኢንቨስትመንት ሊያመራ የሚችል እንጂ፣ በእነሱ በኩል የተገባ መደበኛ ቃል እንዳልሆነ ገልጿል። FSG አሁንም የሊቨርፑልን የሥራ አመራር ቁጥጥር እንደያዘ ይገኛል።
ይሁን እንጂ ይህ ሁኔታ ቤዞስ፣ ብሃቲያ እና የፌስቡክ መስራች የሆነው ቢሊየነሩ ኤድዋርዶ ሳቬሪን በቅርብ ጊዜ ውስጥ FSGን በመተካት የሊቨርፑል አብላጫ ባለቤቶች የመሆን ዕድልን ከፍ ያደርገዋል። በዓለም ላይ ካሉ ባለጸጋዎች አንዱ የሆኑት ቤዞስ፣ እርሳቸው ዋና ባለሀብት በሆኑበት በK5 ስፖርትስ ፈንድ በኩል በ1892 ሆልዲንግስ ውስጥ ድርሻ በመግዛታቸው፣ በዚህ ደረጃ ላይ እንደ “ተገብሮ” (passive) ባለሀብት ነው የሚታዩት። የK5 ግሎባል መስራችና ዋና አጋር የሆኑት ብራያን ባውም ከአሚት ብሃቲያ (ምክትል ሊቀመንበር) እና ከኤድዋርዶ ባለቤት ኢሌን ሳቬሪን ጋር በመሆን በተስፋፋው የሊቨርፑል የዳይሬክተሮች ቦርድ ውስጥ መቀመጫ ይኖራቸዋል።
ብሃቲያ ሊቨርፑልን ለመግዛት የሚረዳውን የገንዘብ ድጋፍ ያገኘው ከሚታል ቤተሰብ ትረስት (Mittal Family Trust) ነው። አማቹ የህንድ የብረት ባላባትና ሌላኛው ቢሊየነር ላክሽሚ ሚታል ናቸው። የሚታል ቤተሰብ ሃብት ወደ 17 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት ሲሆን፣ የሳቬሪን ደግሞ 33 ቢሊዮን ዶላር ገደማ እንደሆነ ይገመታል።