League Table

በካይ ሃቨርትዝ የግንባር ግብ አርሰናል በርንሌይን አሸንፎ ለዋንጫው ተቃረበ

የጉጉት እና የተስፋ ድባብ በአርሰናል ስጋት የታጀበበት ምሽት ነበር። ጨዋታው ቀጥተኛ እና ቀላል ይሆንልናል ተብሎ ቢታሰብም ነገሮች ግን እንደተጠበቁት አልነበሩም። በርንሌይ ከፕሪሚየር ሊጉ መውረዱ በሚያዝያ 14 (April 22) የተረጋገጠ ቢሆንም፣ አሰልጣኙን ስኮት ፓርከርን አሰናብቶ በጊዜያዊ አሰልጣኝ ማይክል ጃክሰን እየተመራ ወደ ኤምሬትስ መጣ። ባለፉት አስር የሊግ ጨዋታዎች ሶስት ጊዜ ብቻ አቻ የወጣው በርንሌይ፣ ለአርሰናል ግን ቀላል አልነበረም። መድፈኞቹ ከትልቅ ውድቀት ስጋት ጋር ሲታገሉ አምሽተዋል። የማርጂኑ ጥበት በሁለተኛው አጋማሽ ላይ ከፍተኛ ጭንቀት ፈጥሮ ነበር፤ ማንኛውም የበርንሌይ ድንገተኛ ጥቃት ውጤቱን ሊቀይረው እንደሚችል ሁሉም ያውቅ ነበር። አርሰናል ከ2004 በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ የሊጉን ዋንጫ ለማንሳት የሚያደርገው ጉዞ እጅግ አድካሚ እና የነርቭ ፍልሚያ የበዛበት ነው።

የዋንጫው መስመር አሁንም በቅርብ ርቀት ላይ ይገኛል። ማንቸስተር ሲቲ ማክሰኞ ምሽት ከበርንማውዝ ጋር በሚያደርገው ጨዋታ ነጥብ የሚጥል ከሆነ የዋንጫው ጉዳይ እዚሁ ያበቃል። ሲቲ ነጥቦቹን የሚያገኝ ከሆነ ግን የዋንጫው ባለቤት በመጨረሻው እሁድ አርሰናል ከክሪስታል ፓላስ፣ ሲቲ ደግሞ ከአስቶን ቪላ ጋር በሚያደርጉት ጨዋታ ይለያል። አርሰናል በርንሌይን ለማሸነፍ በሁለቱ ጠንካራ ጎኖቹ ላይ ተመስርቷል፤ በቆመ ኳስ የሚገኝ ግብ እና ድንቅ የመከላከል ብቃት። በመጀመሪያው አጋማሽ መገባደጃ ላይ ቡካዮ ሳካ ያሻማውን የማዕዘን ኳስ ካይ ሃቨርትዝ በግንባሩ በመግጨት ያስቆጠራት ግብ ብቸኛ ሆና ዘልቃለች። ይህም ለቡድኑ በውድድር ዘመኑ 19ኛውን ያለግብ የወጣበት (clean sheet) ጨዋታ ሆኖ ተመዝግቧል።

አርቴታ በኤምሬትስ ስታዲየም የ20 ዓመት ታሪክ ውስጥ ትልቁ በሚባለው በዚህ ጨዋታ ደጋፊዎች በነቂስ ወጥተው ቡድኑን እንዲያበረታቱ ጥሪ አቅርቦ የነበረ ሲሆን፣ ደጋፊዎቹም በስታዲየሙ ዙሪያ ቀይ ጢሶችን በማጨስ ለቡድኑ ያላቸውን አጋርነት አሳይተዋል። አርቴታ በምርጫው ላይ ድፍረት የተሞላበት ውሳኔ አስተላልፏል፤ ማርቲን ኦዴጋርድ እና ኢበረቺ ኢዜን ከዲክላን ራይስ ፊት ለፊት በመሃል ሜዳ ላይ አሰልፏል። በዘጠኝ ቁጥር ሚና ደግሞ ከቪክቶር ጂዮከሬስ ይልቅ ሃቨርትዝን መርጧል። አርሰናል የበርንሌይን የተደራጀ መከላከያ ለመስበር ከፍተኛ ጥረት አድርጓል። የበርንሌይ ተጫዋቾች ኳስ ለማስጀመር ጊዜ በሚያባክኑበት ወቅት የቤት ደጋፊዎች ተቃውሞአቸውን ያሰሙ ነበር። የቀድሞው የቶተንሃም ተጫዋች እና የበርንሌይ ካፒቴን ካይል ዎከር በደጋፊዎች ዘንድ የተለመደው ተቃውሞ ሲደርስበት ነበር።

አርሰናል ቀድሞ ግብ ለማግኘት ቢጣጣርም አልተሳካለትም ነበር። በ15ኛው ደቂቃ ላይ ሌአንድሮ ትሮሳርድ ከኢዜ ያገኘውን ኳስ ይዞ በመግባት የመታው ኳስ በግቡ ቋሚ ተመልሷል። አርቴታ ሪካርዶ ካላፊዮሪን ከመስመር ተከላካይነት ወደ ውስጥ እንዲገባ በማዘዝ የበርንሌይን መከላከያ ለማስከፈት ሞክሯል። በ27ኛው ደቂቃ ላይ በርንሌይዎች አደገኛ ጥቃት ሰንዝረው የነበረ ቢሆንም ሀኒባል ሜብሪ ያገኘውን አጋጣሚ ሳይጠቀምበት ቀርቷል። ቡካዮ ሳካ በሳጥን ውስጥ ተጥሎ የነበረ ቢሆንም በቪኤአር (VAR) ታይቶ ቅጣት ምት ሳይሰጥ ቀርቷል። በመጨረሻም ኦዴጋርድ የመታው ኳስ ተከላካይ ነክቶ በወጣው የማዕዘን ኳስ አማካኝነት ሃቨርትዝ ግቧን አስቆጥሮ ስታዲየሙን በደስታ አናውጦታል።

በሁለተኛው አጋማሽ በርንሌይዎች ተሻሽለው የቀረቡ ሲሆን፣ ኢዜ ያገኘውን አጋጣሚ ተጠቅሞ የመታው ኳስ የግቡን አግዳሚ ታክኮ ወጥቷል። ጨዋታው ለአርሰናል ደጋፊዎች እጅግ አስጨናቂ በሆነ ሁኔታ ቀጥሎ ነበር። በ67ኛው ደቂቃ ላይ ሃቨርትዝ በኡጎቹኩ ላይ በሰራው ጥፋት በቀይ ካርድ ሊሰናበት ይችል የነበረ ቢሆንም በቢጫ ካርድ እንዲቀጣ ተወስኗል። የመጨረሻዎቹ ደቂቃዎች ለአርሰናል እጅግ አስፈሪ ቢሆኑም፣ ቡድኑ እንደለመደው ሳይረታ እና ነጥቡን ሳይሰጥ ጨዋታውን አጠናቋል።