አማካዩ ባለፉት ጥቂት ሳምንታት በካራባኦ ካፕ ፍጻሜ በሲቲ ከመሸነፍ ጀምሮ ቡድኑ “ውጣ ውረድ” ውስጥ እንደነበረ ገልጿል። አርሰናል በኤፍኤ ካፕ በሳውዝሃምፕተን ተሸንፎ ሲወጣ፣ በሊጉ ደግሞ በሜዳው በቦርንማውዝ መሸነፉ ይታወሳል። ከዚያ በፊት ግን በሻምፒዮንስ ሊግ ሩብ ፍጻሜ የመጀመሪያ ጨዋታ ስፖርቲንግን 1-0 አሸንፈው፣ ረቡዕ እለት በኤምሬትስ 0-0 በሆነ አቻ ውጤት በማጠናቀቅ ከአትሌቲኮ ማድሪድ ጋር ለግማሽ ፍጻሜ ቀጠሮ ይዘዋል።
ራይስ ከስፖርቲንግ ጋር በነበረው የሁለተኛው ዙር ጨዋታ ላይ የታዩትን ጠንካራ የመከላከል ጎኖች አድንቋል። ነገር ግን ቡድኑ ኳስን በመቆጣጠር ረገድ ስላሳየው ድክመት በግልጽ ተናግሯል፤ ይህም ባለፉት አምስት ጨዋታዎች በግልጽ የታየ ነበር። አርሰናል የተሻለ ብቃት ማሳየት አለበት ወይ ተብሎ ሲጠየቅ፣ ራይስ “አዎ፣ በእርግጠኝነት” በማለት መለሰ። “ይህንን እንደ ቡድን እናውቃለን። ነገሮችን አድበስብሶ ማለፍ አያስፈልግም። ከቦርንማውዝ ጋር ካደረግነው ጨዋታ የተሻለ ብቃት ማሳየት አለብን። ረቡዕ ከስፖርቲንግ ጋር በነበረው ጨዋታም ቢሆን እንዲሁ። በመከላከል ረገድ ግን በጣም የተሻልን ነበርን። ከዚህ ቀደም ባልነበረ ሁኔታ በቅርብ ጊዜያት ብዙ ስህተቶችን ስንሰራ ነበር። ነገር ግን ያንን ማስቀረት ችለናል፤ ይህም ጥሩ ነው” ብሏል።
“ዋናው ነገር መሰረታዊ ነገሮችን በተሻለ ደረጃ መስራት ነው… በቸልተኝነት የምናባክናቸውን የአምስትና የአስር ሜትር ቅብብሎችን ማስተካከል ያስፈልጋል። እንዲሁም ኳስን የመቆጣጠር በራስ መተማመንን ማሳደግ፣ ኳስን በረጋ መንፈስ መያዝ እና ጫና ውስጥ አለመሆን አስፈላጊ ነው። ኢቲሃድ ትልቁ የፈተና ሜዳ ነው፤ እኛም የምንጫወተው ለእንዲህ አይነት ግጥሚያዎች ነው። ስለዚህ ጨዋታውን በጉጉት እንጠብቃለን” በማለት ራይስ ተናግሯል።
ራይስ በንግግሩ ለድል ያለውን ተነሳሽነት የገለጸ ሲሆን፣ እሁድ በሚደረገው ጨዋታ በካራባኦ ካፕ ፍጻሜ ለደረሰባቸው ሽንፈት የአጸፋ ምላሽ የመስጠት ፍላጎት እንዳለም አልሸሸገም። የአርሰናል ተጨዋቾች ሲቲ ዋንጫውን ሲያነሳ በዌምብሌይ ሜዳ ላይ ቆመው የተመለከቱ ሲሆን፣ ያ ህመም አሁንም አልለቀቃቸውም፡፡ “በዚያን ቀን እነሱ የተሻሉ ነበሩ” ሲል ራይስ አምኗል። “ውስጥ ገብተን ያንን ክብር አለማሳየት ስህተት ይሆን ነበር። ነገር ግን እነሱ ዋንጫውን ሲያነሱ ማየት ያማል። በመጪው ቅዳሜና እሁድ ያንን ስሜት ለመቀየር በውስጣችን ትልቅ እሳት አለ። በፕሪሚየር ሊጉ ስድስት ጨዋታዎች የቀሩን ሲሆን፣ ጨዋታው ምን ያህል ትልቅ እንደሆነ እናውቃለን።”
“ይህ በጣም የሚያስደስት ነው። ህጻን ሆነህ ፕሪሚየር ሊግን ስትመለከት፣ እነዚህን ትልልቅ ጨዋታዎች እና የዋንጫውን አቅጣጫ የሚወስኑ ወሳኝ ጊዜያትን ታያለህ። አሁን ደግሞ ዝግጁ ነህ ወይ? እና ምን ያህልስ ትፈልገዋለህ? የሚለው ወሳኝ ይሆናል። እዚያ ሄዶ ማሸነፍ ትልቅ ትርጉም ይኖረዋል። ተመልከቱ፣ እነዚህ ልጆች ዝግጁ ናቸው። እንደ ቡድን ተነጋግረናል። ምን እንደሚያስፈልግ እናውቃለን።”
አርሰናል ባለፉት አምስት ጨዋታዎች ሶስት ጎሎችን ብቻ ነው ያስቆጠረው፤ ራይስም ቡድኖች በብዛት የሚጠቀሙበትን የተከላካይ ቁጥር ማብዛት (low block) ማለፍ አስቸጋሪ እንደሆነ ጠቁሟል። ለምሳሌ ስፖርቲንግ ረቡዕ እለት በ 5-3-2 የጨዋታ ስልት ተከላክሏል። ሆኖም ይህ የሲቲ ስልት አይደለም፤ አርሰናል በካራባኦ ካፕ ፍጻሜ ላይ በሲቲ ላይ ምንም አይነት ጫና መፍጠር አልቻለም ነበር። “ጎሎችን ባለማስቆጠራችን ምክንያት ምናልባትም ብዙ ትኩረት እና ትችት እየደረሰብን እንደሆነ ይሰማኛል” ብሏል ራይስ። “ባለ አምስት ተከላካይ ቡድኖችን መግጠም ከባድ ነው፤ በዚህ የውድድር ዘመን ከምንጊዜውም በላይ 5-4-1 እና 5-3-2 የሚጠቀሙ ቡድኖችን ገጥመናል። ቡድኖች በእኛ ላይ ያላቸው አሰላለፍ የተለየ ነው።”
“ያንን ሰብሮ መግባት የኛ ስራ ነው፤ ነገር ግን በተከላካይ ክልላቸው ተጠቅጥቀው ሲቆሙ፣ ከአለም አቀፍ ደረጃ ተጫዋቾች ጋር ስለሆነ የምትጫወተው አንዳንድ ጊዜ ከባድ ይሆናል። ስለዚህ ነገሩን ከተለየ እይታ ማየት ያስፈልጋል። ደጋፊዎች ተጨማሪ ነገር ማየት እንደሚፈልጉ አውቃለሁ፤ ነገር ግን ምናልባትም ረቡዕ እለት… ማለፋችን ብቻ ትልቅ ስኬት ነው” ብሏል።
ራይስ ሰኞ እና ማክሰኞ በህመም ተኝቶ ስለነበር የመሰለፉ ጉዳይ አጠራጣሪ ነበር። ጨዋታው ከ24 ሰዓት በፊት ቢሆን ኖሮ መሰለፍ እንደማይችልም ተናግሯል። ለእንግሊዝ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ቶማስ ቱሄል “ለረጅም ጊዜ ምቾት ማጣት” እንደነበረበት እና “70%” ብቃት ላይ ብቻ እንደነበረ በመግለጽ የመጋቢት ወር የብሄራዊ ቡድን ጨዋታዎችን እንዲያመልጠው ያደረገው ይህ አድካሚ ወቅት ለራይስ ከባድ ነበር።
ራይስ ከብሄራዊ ቡድን ጨዋታ በኋላ የነበረውን የሳውዝሃምፕተን ጨዋታ አምልጦታል፤ ነገር ግን አሁን ሁሉም ተጫዋች የሚያስፈልግበት ወቅት መሆኑን ስለሚያውቅ፣ በተለይም አርሰናል እንደ ዩሪየን ቲምበር፣ ማርቲን ኦዴጋርድ እና ቡካዮ ሳካ ያሉ ቁልፍ ተጫዋቾችን በጉዳት ባጣበት በዚህ ወቅት ጠንክሮ ለመጫወት ቆርጧል። “እነዚያ ተጫዋቾች እንዲመለሱ እንፈልጋለን፤ ያስፈልጉናል። እነሱ ከቡድናችን ትልልቅ እና ምርጥ ተጫዋቾች መካከል ሶስቱ ናቸው። በዚህ አመት በትልልቅ ጨዋታዎች በጣም ናፍቀውናል። እኔ ለሁለት ቀናት ታምሜ አልጋ ላይ ነበርኩ። ነገር ግን ረቡዕ ጠዋት ተሻለኝ። 100% ብቃት ላይ ባልሆንም ቡድኑን መርዳት ፈልጌ ነበር። በማንኛውም ሁኔታ ውስጥ ለዚህ ክለብ መጫወት ማለት ይህ ነው” ብሏል።