በርንሌይ ባወጣው መግለጫ “በዛሬው የፕሪሚየር ሊግ ጨዋታ ማጠቃለያ ላይ በሀኒባል ላይ በተሰነዘረው የዘረኝነት ጥቃት መላው የበርንሌይ እግር ኳስ ክለብ አባላት ተጸይፈዋል። ይህ በህብረተሰባችን ውስጥ ቦታ የለውም፤ ድርጊቱንም ያለ ምንም ገደብ እናወግዛለን። ክለባችን ለማንኛውም አይነት አድልዎ ‘ዜሮ ታለራንስ’ (ምንም ዓይነት ትዕግስት የሌለው) አቋም አለው። ክለቡ ጉዳዩን ለኢንስታግራም ባለቤት ሜታ ሪፖርት ያደረገ ሲሆን፣ ከእነሱ፣ ከፕሪሚየር ሊጉ እና ከፖሊስ ጋር በመሆን ጥፋተኛው ተለይቶ እንዲመረመር ጠንካራ ድጋፍ ይጠብቃል። ሀኒባል ከክለቡም ሆነ ጥቃቱን ማውገዝ ከጀመሩት የበርንሌይ ደጋፊዎች ሙሉ ድጋፍ ያገኛል። ለዘረኝነት ምንም ቦታ የለም” ብሏል።
ቼልሲ በበኩሉ በዌስሊ ፎፋና ላይ በደረሰው አስነዋሪ የዘረኝነት ጥቃት “መደንገጡን እና መጸየፉን” ገልጿል። “ዛሬ ከበርንሌይ ጋር ከተደረገው ጨዋታ በኋላ በዌስ ላይ የተፈጸመው ያነጣጠረ የዘረኝነት ጥቃት አስጸያፊ እና ፈጽሞ የማይታገስ ነው። እንዲህ ዓይነቱ ባህሪ ሙሉ በሙሉ ተቀባይነት የሌለው እና ከእግር ኳስ እሴቶች እንዲሁም ክለባችን ከሚወክላቸው መርሆዎች ጋር የሚቃረን ነው። ለዘረኝነት ምንም ቦታ የለም። እኛ ከዌስ ጎን በጽናት እንቆማለን። ስራቸውን በመስራታቸው ብቻ እንዲህ ያለ ጥላቻ እንዲደርስባቸው ለሚገደዱ ተጫዋቾቻችን ሁሉ ሙሉ ድጋፍ እናደርጋለን። አጥፊዎቹን በመለየት ረገድ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመሆን ጠንካራ እርምጃ እንዲወሰድ እንሰራለን” ብሏል።
የፎፋና ጥቃት ይፋ ከመሆኑ በፊት የፕሪሚየር ሊጉ ባወጣው መግለጫ “በሀኒባል ላይ የተሰነዘረውን አስጸያፊ የዘረኝነት ጥቃት በማውገዝ ከበርንሌይ ጎን እንቆማለን፤ ለተጫዋቹ እና ለክለቡም ሙሉ ድጋፋችንን እንሰጣለን። እግር ኳስ ለሁሉም ነው፤ በእግር ኳሳችንም ሆነ በማንኛውም ህብረተሰብ ውስጥ ለአድልዎ ቦታ የለም። ጥፋተኛ ሆነው የተገኙ ግለሰቦች ከክለብ መታገድን እና የህግ ክስን ጨምሮ ከባድ ቅጣት ይጠብቃቸዋል” ሲል አስታውቋል።