በተጨማሪም በጨዋታው ወቅት ደጋፊዎች ቁሳቁሶችን ወደ ሜዳ በመወርወራቸው ዩኢኤፍኤ ክለቡን የ2,250 ዩሮ ተጨማሪ ቅጣት ቀጥቶታል። ቶትንሃም በፍራንክፈርት የተደረገውን ጨዋታ 2-0 በማሸነፍ ወደ ቀጣዩ 16ቱ ዙር ያለፈ ሲሆን፣ በዚያም ከአትሌቲኮ ማድሪድ ጋር እንደሚገናኝ ታውቋል። የዩኢኤፍኤ የቁጥጥር፣ የሥነ-ምግባር እና የዲሲፕሊን አካል በሰጠው ውሳኔ፣ በደጋፊዎች ዘረኛ እና አድሎአዊ ባህሪ ምክንያት ክለቡ ለቀጣዩ አንድ የዩኢኤፍኤ ውድድር የሜዳ ውጭ ደጋፊዎች ትኬት እንዳይሸጥ ቢታገድም፣ እገዳው ለአንድ አመት የሙከራ ጊዜ እንዲዘገይ ተወስኗል።
ቶትንሃም ባወጣው መግለጫ “ክለቡ ከዩኢኤፍኤ ምርመራ እንዲሁም ከጀርመን እና ከለንደን ሜትሮፖሊታን ፖሊስ ጋር ሙሉ ትብብር አድርጓል። ለኢንትራክት ፍራንክፈርት ደጋፊዎች የናዚ ሰላምታ ሲያሳዩ የተገኙት ሶስቱም ግለሰቦች ተለይተው የታወቁ ሲሆን፣ በክለቡ የቅጣት ደንብ መሰረት ያልተገደበ እገዳ ተጥሎባቸዋል” ብሏል። አክሎም “ክለባችን ማንኛውንም ዓይነት መድልዎ አጥብቆ ይቃወማል፣ በዚህም ምክንያት ጠንካራውን እርምጃ ወስደናል። በዚያ ምሽት በጥቂት ደጋፊ ነን ባዮች የታየው አሳፋሪ ባህሪ የክለባችንን እና የደጋፊዎቻችንን እሴት በምንም መልኩ አይወክልም” ሲል ገልጿል።