ዶውማን በጥር ወር ከአርሰናል ጋር የቅድመ-ኮንትራት ስምምነት የተፈራረመ ሲሆን፣ ይህም ታህሳስ 31 ቀን 17 ዓመት ሲሞላው በራሱ ጊዜ ወደ መጀመሪያው ፕሮፌሽናል ኮንትራት ይቀየራል። የእነዚህ ስምምነቶች የህግ ጉዳዮች ‘ኦንሳይድ ሎው’ (Onside Law) በተባለ የስፖርት፣ ሚዲያ እና መዝናኛ የህግ ተቋም የተከናወኑ ሲሆን፣ ሮብ እና ኢታን ዶውማንም በወደፊት የውል ድርድሮች ላይ ክንፍ ተጫዋቹን የመወከል መብት አላቸው። ፊፋ ከዐስር ዓመታት በፊት የወኪል ፈቃድ አሰጣጥ ስርዓቱን ካላላ በኋላ፣ ምርጥ ተጫዋቾች በቤተሰቦቻቸው መወከላቸው እያደገ የመጣ አዝማሚያ ቢሆንም የዶውማን ቤተሰቦች ግን ከሌሎች በተሻለ ብቁ ሆነው ተገኝተዋል።
ሮብ ዶውማን የታችኛው እርከን አሰልጣኝ ከመሆናቸው በተጨማሪ ‘ፓንቲዮን ስፔሻሊቲ’ (Pantheon Speciality) የተባለ የኢንሹራንስ ኩባንያ መስራች እና ዋና ስራ አስፈፃሚ ሲሆኑ፣ ታላቅ ልጃቸው ኢታን ደግሞ ከኖቲንግሃም ዩኒቨርሲቲ በኢኮኖሚክስ ተመርቆ በኢንሹራንስ ደላላነት በመስራት ላይ ይገኛል። ሁለቱም በ2003 በዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር (ፊፋ) በድጋሚ የተዋወቀውን እና በመጀመሪያው ዙር 52 በመቶ ብቻ ያለፉበትን የፈተና ሂደት አልፈው የፊፋ ወኪል ፈቃድ አግኝተዋል።
የዶውማን የቅርብ ጊዜ ትኩረት በአርሰናል የሚያሳየውን እድገት መቀጠል እና በዚህ ክረምት የሚሰጠውን የጂ.ሲ.ኤስ.ኢ (GSCE) ፈተና በጥሩ ውጤት ማጠናቀቅ ነው። ምንም እንኳን ከአዲዳስ ጋር የትጥቅ ስምምነት ቢፈራረምም እና ከኢያን ራይት ጋር በአንድ ማስታወቂያ ላይ ቢታይም፣ ቤተሰቡ ተጨማሪ የንግድ ስምምነቶችን ለማግኘት ምንም ዓይነት ጥድፊያ የለባቸውም።