League Table

የቀድሞው የአርሰናል ግብ ጠባቂ አሌክስ ማኒንገር በ48 ዓመቱ በድንገተኛ አደጋ ከዚህ ዓለም ተለየ

በ1998 አርሰናል የፕሪሚየር ሊጉን እና የኤፍኤ ካፕ ዋንጫዎችን (ደብል) እንዲያሸንፍ የረዳው የቀድሞው ኦስትሪያዊ ግብ ጠባቂ አሌክስ ማኒንገር፣ በ48 ዓመቱ በኦስትሪያ በደረሰ የትራፊክ አደጋ መሞቱ ተሰምቷል። የመጀመሪያ ክለቡ የሆነው ሬድ ቡል ሳልዝበርግ ይህን አሳዛኝ ዜና ሐሙስ ዕለት ይፋ አድርጓል። የኦስትሪያው ቡንደስሊጋ ክለብ በይፋዊ የኤክስ (X) ገጹ ላይ ባሰፈረው መልዕክት፡ “በደረሰበት የትራፊክ አደጋ ሕይወቱ በድንገት ያለፈውን የቀድሞ ግብ ጠባቂያችንን አሌክሳንደር ማኒንገርን እናዝናለን። ሐሳባችን እና ጸሎታችን ከቤተሰቦቹና ከጓደኞቹ ጋር ነው፤ አሌክሳንደር በሰላም እረፍ” ብሏል።

ከኦስትሪያ የወጡ ዘገባዎች እንደሚጠቁሙት፣ የማኒንገር መኪና ሐሙስ ረፋድ ላይ በኑስዶርፍ አም ሃውንስበርግ አካባቢ በሚገኝ የባቡር ማቋረጫ ላይ ከባቡር ጋር ተጋጭቷል። አርሰናልም ለማኒንገር በሰጠው መግለጫ፡ “በዚህ እጅግ አሳዛኝ ወቅት ሐሳባችን ሁሉ ከቤተሰቦቹና ከወዳጆቹ ጋር ነው። ነፍሱን በሰላም ያሳርፈው” ሲል ሐዘኑን ገልጿል።

ለኦስትሪያ ብሔራዊ ቡድን 33 ጨዋታዎችን ያደረገው ማኒንገር፣ በሰኔ 1997 በ500,000 ፓውንድ ከግራዘር ኤኬ ወደ መድፈኞቹ ነበር የተቀላቀለው። በአርሰን ቬንገር ስር ለ5 ዓመታት በቆየባቸው ጊዜያት 64 ጨዋታዎችን ያደረገ ሲሆን፣ የፕሪሚየር ሊግ ዋንጫንም ማሸነፍ ችሏል። ሆኖም በዴቪድ ሲማን እና በሪቻርድ ራይት ፉክክር ምክንያት የመሰለፍ ዕድል በማጣቱ ወደ ስፔኑ ኢስፓንዮል አምርቷል። በተጨማሪም በጣሊያኑ ቶሪኖ፣ ቦሎኛ፣ ሲዬና እና ጁቬንቱስ፣ እንዲሁም በጀርመኑ ኦግስበርግ ተጫውቷል።

በመቀጠልም ወደ እንግሊዝ ከፍተኛ ሊግ በመመለስ በሊቨርፑል ለአጭር ጊዜ ቆይታ አድርጓል። በሐምሌ 2016 ሊቨርፑልን የተቀላቀለው ማኒንገር፣ ምንም እንኳን በክለቡ የመጨረሻ የውድድር ዘመኑ በይፋዊ ጨዋታዎች ላይ ባይሰለፍም፣ ሊቨርፑል በኤክስ ገጹ፡ “ሊቨርፑል እግር ኳስ ክለብ በቀድሞ ግብ ጠባቂያችን አሌክስ ማኒንገር በ48 ዓመቱ ከዚህ ዓለም በሞት መለየት እጅግ አዝኗል። በሊቨርፑል ውስጥ ያለን ሁላችንም በዚህ አስቸጋሪ ወቅት ከቤተሰቦቹና ከወዳጆቹ ጋር ነን” ሲል የሐዘን መግለጫ አውጥቷል።

የኦስትሪያ እግር ኳስ ማኅበርም ማኒንገር “ምርጥ” ተጫዋች እንደነበር ገልጾ ሐዘኑን ገልጿል። የማኅበሩ ስፖርት ዳይሬክተር ፒተር ሾትል በድረ-ገጻቸው ላይ እንደገለጹት፡ “አሌክሳንደር ማኒንገር በሜዳ ውስጥም ሆነ ከሜዳ ውጭ የኦስትሪያ እግር ኳስ ድንቅ አምባሳደር ነበር። በአውሮፓ በነበረው የእግር ኳስ ሕይወቱ አርአያ በመሆን በርካታ ወጣት ግብ ጠባቂዎችን አነሳስቷል። ሙያዊ ብቃቱ፣ እርጋታው እና ታማኝነቱ ለቡድኖቹም ሆነ ለብሔራዊ ቡድኑ ትልቅ ዋጋ ነበረው። ያስመዘገባቸው ስኬቶች ከፍተኛ ክብር የሚገባቸውና የማይረሱ ናቸው። በዚህ አስቸጋሪ ወቅት ሐሳባችን ከቤተሰቦቹና ከወዳጆቹ ጋር ነው” ብለዋል።