ሊቨርፑል እሁድ ዕለት ከቶተንሃም ጋር ባደረገው ጨዋታ በመጨረሻ ሰዓት ግብ ተቆጥሮበት ነጥብ ከጣለ በኋላ በደጋፊዎች ተቃውሞ አስተናግዷል። ዶሚኒክ ሶቦዝላይ ደጋፊዎች ስታዲየሙን ቀድመው መልቀቃቸው በቡድኑ ላይ ተፅዕኖ ማሳደሩን ቢናገርም፥ ስሎት ግን ተቃውሞው በቀጥታ በእርሳቸው ላይ ያነጣጠረ መሆኑን አይቀበሉም።
“ደጋፊዎች ሲበሳጩ ማየት ደስ አይልም፤ ምክንያቱም አሸንፈህ አታውቅም” ያሉት ስሎት፥ በጡንቻ ጉዳት የቶተንሃሙን ጨዋታ ያለፈው ኢብራሂማ ኮናቴ እንደሚመለስ ይጠብቃሉ። አክለውም “ወደዚህ ክለብ ስመጣ ሰዎች የነገሩኝ ነገር ቢኖር፥ ይህ ክለብ ከሌሎች እንደሚለይ እና ደጋፊዎቹ አሰልጣኙን ለረጅም ጊዜ እንደሚደግፉ ነው። ስለዚህ የምትሉት ነገር እውነት ከሆነ – እኔ ግን ይህ አይሰማኝም – ብዙ ስህተቶችን ሰርቻለሁ ማለት ነው፤ ይህም ደስ የሚል ስሜት አይደለም። በመልካምም ሆነ በመጥፎ ጊዜ አሰልጣኙን በሚደግፍ ክለብ ውስጥ ሆኜ በእኔ ደስተኛ ካልሆኑ፥ ብዙ ነገሮችን ተሳስቻለሁ ማለት ነው። ነገር ግን የእግር ኳስ ኢንዱስትሪ እንዴት እንደሚሰራ አውቃለሁ። ማሸነፍ ብዙ ነገሮችን ሊቀይር ይችላል። ነገ ለማሳካት የምንሞክረውም ይህንኑ ነው፤ ለዚህም ሙሉ በሙሉ ዝግጁ ነን” ብለዋል።
ስሎት ስለሰሯቸው ስህተቶች በዝርዝር ባይገልጹም፥ በስራ ፍላጎት እና ዕድሎችን በመፍጠር ረገድ ሊቨርፑል አሁንም ከብዙ ተቃዋሚዎቹ እንደሚበልጥ አጥብቀው ተናግረዋል። “ሊጉን ባሸነፍንበት የውድድር ዘመን እንኳን የተሳሳቱ ውሳኔዎችን አስተላልፌያለሁ። ነገር ግን የወሰንኳቸው ውሳኔዎች ሁሉ አንድ አይነት ዓላማ ነበራቸው፤ እሱም ጨዋታውን እንድናሸንፍ መርዳት ነው። በመራኋቸው ጨዋታዎች ከ80 እስከ 90 በመቶ የሚሆኑት ቡድኖቼ ከሌላው ቡድን በላይ ጠንክረው ሰርተዋል፤ እንዲሁም የተሻሉ የጎል ዕድሎችን ፈጥረዋል” ሲሉ ክለባቸውን ተከላክለዋል።
ሊቨርፑል በዚህ የውድድር ዘመን በጋላታሳራይ ሁለት ጊዜ ቢሸነፍም፥ አሰልጣኙ ግን ወደ ሩብ ፍፃሜ አልፎ ከፓሪስ ሴንት ዠርሜን ወይም ከቼልሲ ጋር የመገናኘቱ ዕድል በአንፊልድ የተለየ ውጤት እንደሚያመጣ ያምናሉ። “የዚህን ጨዋታ አስፈላጊነት እንረዳለን” ያሉት ዋና አሰልጣኙ፥ “ወደ ቻምፒዮንስ ሊግ ሩብ ፍፃሜ መድረስ እንችላለን። ይህ ለእኔ የመጀመሪያዬ ስለሚሆን ልዩ ትርጉም ይኖረዋል። ክለቡ ከዚህ ቀደም በተደጋጋሚ ቢያሳካውም፥ የቻምፒዮንስ ሊግ ሩብ ፍፃሜን እንደ ቀላል ነገር አንመለከተውም” በማለት ንግግራቸውን አጠቃለዋል።