ከመንግስት ጋር በተደረገ ምክክር የፕሪሚየር ሊጉ አመራሮች ከሶስት ዓመት በፊት በፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ እገዳን ተግባራዊ ለማድረግ ተስማምተው ነበር። ክለቦች አዳዲስ ስፖንሰሮችን እንዲፈልጉ ጊዜ ለመስጠት እገዳው እስከ ቀጣዩ የውድድር ዘመን መጀመሪያ ድረስ እንዲዘገይ ተደርጓል። ይሁን እንጂ የቁማር ድርጅቶች ከገበያው መውጣታቸው በክለቦች መካከል ዝቅተኛ ዋጋ ባላቸው ስፖንሰሮች ላይ ከፍተኛ ፉክክር እንዲፈጠር አድርጓል። በዚህ የውድድር ዘመን የቁማር ድርጅቶች ስፖንሰር ከሆኑላቸው 10 ክለቦች መካከል ቦርንማውዝ ብቻ ምትክ ማግኘቱን ያሳወቀ ሲሆን፣ የስታዲየም ስፖንሰሩ ቫይታሊቲ (Vitality) በዝቅተኛ ዋጋ ወደ ማሊያው ፊት ለፊት ተዛውሯል። ይህ ሁኔታ በሌሎች ክለቦችም ሊደገም እንደሚችል ይገመታል።
ብሬንትፎርድ አሁን ያለውን የልምምድ ትጥቅ ስፖንሰር ‘ኢንዲድ’ (Indeed) የተሰኘውን የሥራ ፈላጊ ድረ-ገጽ በቀጣይ የውድድር ዘመን በማሊያው ፊት ለፊት ለማድረግ ከስምምነት መድረሱ ታውቋል። ሁለቱም ክለቦች (ቦርንማውዝ እና ብሬንትፎርድ) ከዚህ ቀደም ከቢጄ88 (bj88) እና ሆሊውድ ቤትስ (Hollywood Bets) ጋር ከነበራቸው ስምምነት የ50 በመቶ ቅናሽ መቀበላቸው ተሰምቷል። አዲሶቹ ስምምነቶች በዓመት ከ4 እስከ 5 ሚሊዮን ፓውንድ የሚያወጡ ሲሆን፣ ይህም የገበያውን መዳከም በግልጽ ያሳያል። ይሁን እንጂ ኤቨርተን እና ፉልሃም ከዚህ በተለየ ሁኔታ ሲኤምሲ ማርኬትስ (CMC Markets) ከተባለው የውጭ ምንዛሬ ነጋዴ ድርጅት ጋር የላቀ ድርድር ላይ ናቸው። ይህም ከስቴክ (Stake) እና ኤስቢኦቤት (SBOBET) ጋር ከነበራቸው ውል መጠነኛ ጭማሪ ይኖረዋል። ሌሎች ሰባት የቁማር ድርጅቶች የሚደግፏቸው ክለቦች ግን አሁንም ስፖንሰር በመፈለግ ላይ ናቸው።
በተጨማሪም ቼልሲ እና ኒውካስል ከ አይኤፍኤስ (IFS) እና ሴላ (Sela) ጋር ያላቸው ውል በበጋው ስለሚጠናቀቅ አዳዲስ ስፖንሰሮችን እየፈለጉ ነው። ቼልሲ ባለፉት ሶስት የውድድር ዘመናት መጀመሪያ ላይ ያለ ስፖንሰር የቆየ ሲሆን፣ በኋላ ላይ የአጭር ጊዜ ስምምነቶችን የማድረግ ስልቱ በሚሊዮኖች የሚቆጠር ገቢ እንዲያጣ አድርጎታል። የቁማር ድርጅቶች ከገበያው መውጣታቸው በታላላቆቹ ስድስት ክለቦች እና በሌሎች የፕሪሚየር ሊግ ክለቦች መካከል ያለውን ከፍተኛ የገቢ ልዩነት ይበልጥ አባብሶታል። አርሰናል፣ ሊቨርፑል፣ ማንቸስተር ሲቲ እና ማንቸስተር ዩናይትድ ከኤምሬትስ፣ ስታንዳርድ ቻርተርድ፣ ኢቲሃድ ኤርዌይስ እና ስናፕድራጎን ጋር በዓመት ከ50 እስከ 60 ሚሊዮን ፓውንድ የሚያወጡ የረጅም ጊዜ ውሎች አሏቸው። የቶተንሃም ከኤአይኤ (AIA) ኢንሹራንስ ጋር ያለው የ40 ሚሊዮን ፓውንድ ውል በቀጣይ የውድድር ዘመን መጨረሻ ያበቃል።
ሊድስ እና ብራይተን ከሬድ ቡል እና አሜሪካን ኤክስፕረስ ጋር የረጅም ጊዜ ውል ቢኖራቸውም፣ የተቀሩት ክለቦች የማሊያ ስፖንሰር ድርድር ፈታኝ ሆኖባቸዋል። አንድ የክለብ ከፍተኛ ስራ አስፈፃሚ ለጋርዲያን ሲናገሩ “ሁሉም ማለት ይቻላል ገንዘብ እያጡ ነው” ብለዋል። “ከታላላቆቹ ስድስት ክለቦች ውጭ የማሊያ ስፖንሰርሺፕ ዋጋ በዓመት ከነበረበት ከ8 እስከ 12 ሚሊዮን ፓውንድ በ50 በመቶ ገደማ ቀንሷል። አንዳንድ ልዩነቶች ሊኖሩ ቢችሉም ገበያው በጣም አስቸጋሪ ነው።” ኤቨርተን እና ዌስትሃም ነባር ስፖንሰሮቻቸውን ስቴክ (Stake) እና ቦይል ስፖርትስ (Boyle Sports) ወደ ተጫዋቾች እጅጌ (sleeve) ለማዛወር ወስነዋል። በእጅጌ ላይ የሚደረጉ የቁማር ድርጅቶች ማስታወቂያ ባለመታገዱ ይህ እንደ አማራጭ ተወስዷል። የኢንግሊዝ እግር ኳስ ሊግ (EFL) የቁማር ስፖንሰርሺፕን አልከለከለም፤ ከስካይ ቤት (Sky Bet) ጋር እስከ 2029 ድረስ ውል አለው። በዚህም ምክንያት በማሊያ ላይ መቆየት የሚፈልጉ የቁማር ድርጅቶች ወደ ታችኛው ሊግ ክለቦች ሊያመሩ ይችላሉ ተብሎ ይጠበቃል።