በውድድር ዘመኑ መጨረሻ ሊቨርፑልን እንደሚለቅ ባለፈው ሳምንት ይፋ ያደረገው የ33 ዓመቱ አጥቂ፥ የግብፅ ብሔራዊ ቡድን ከሳዑዲ አረቢያ እና ስፔን ጋር ባደረጓቸው የወዳጅነት ጨዋታዎች ላይ መሳተፍ አልቻለም። “ፈርኦኖቹ” ማክሰኞ ዕለት በባርሴሎና ከስፔን ጋር ይጫወታሉ።
አጥቂው ለሚደረግለት ህክምና ጥሩ ምላሽ እየሰጠ ሲሆን፥ የአርኔ ስሎት ቡድን የውድድር ዘመኑን እጣ ፈንታ ሊወስኑ የሚችሉ ተከታታይ ጨዋታዎችን በሚጀምርበት በዚህ ወቅት በኢቲሃድ ስታዲየም በሚደረገው ጨዋታ ላይ ይሰለፋል ተብሎ በልበ ሙሉነት እየተጠበቀ ነው።
ባለፈው ታህሳስ ወር በቶተንሃም ጨዋታ ላይ እግሩ ተሰብሮ የነበረው አሌክሳንደር ኢሳክም ለመጀመሪያ ጊዜ ለጨዋታ ዝግጁ ሊሆን ይችላል። ሆኖም በሚቀጥለው ሳምንት ረቡዕ ከፓሪስ ሴንት ዠርሜይን ጋር የሚደረገው የሻምፒዮንስ ሊግ ሩብ ፍፃሜ የመጀመሪያ ዙር ጨዋታ ለሱ መመለሻ የበለጠ አመቺ እንደሆነ ይታሰባል። በ125 ሚሊዮን ፓውንድ የብሪታንያ የዝውውር ሪከርድ የሰበረው ተጫዋች በዚህ ሳምንት ከቡድኑ ጋር ልምምድ ይጀምራል ተብሎ ይጠበቃል።
ስለ ሊቨርፑል አንደኛ ግብ ጠባቂ አሊሰን ቤከር የሚሰማው መረጃ ግን ብዙም የሚያበረታታ አይደለም። ከብራይተን ጨዋታ ዋዜማ የደረሰበት የጅማት ጉዳት አሁንም አላገገመም። ባለፉት የውድድር ዘመናት በተደጋጋሚ የጅማት ጉዳት ሲያጋጥመው የነበረው የ33 ዓመቱ አሊሰን፥ ለፓርክ ዴ ፕሪንስ ጉዞ አሁንም አጠራጣሪ ነው። ባለፈው የውድድር ዘመን ሊቨርፑል በሻምፒዮንስ ሊግ የ16ቱ ዙር የመጀመሪያ ጨዋታ እንዲያሸንፍ በዚሁ ስታዲየም አስደናቂ ብቃት ማሳየቱ ይታወሳል።
በሌላ በኩል ፍሎሪያን ዊርትዝ ወደ ሊቨርፑል ከመጣ በኋላ ካጋጠሙት ችግሮች በመማር ጠንካራ ተጫዋች መሆኑን ገልጿል። ጀርመናዊው ኢንተርናሽናል ባለፈው ክረምት በ116 ሚሊዮን ፓውንድ የክለቡ ሪከርድ በሆነ ዋጋ ከባየር ሌቨርኩሰን የተቀላቀለ ቢሆንም፥ በፕሪምየር ሊጉ አራት ጎሎችን እና ሁለት አሲስቶችን በማድረግ ራሱን ለማስመስከር ሲታገል ቆይቷል።
ለጀርመኑ ስፖርት ሻው (Sportschau) ቴሌቪዥን ፕሮግራም የተናገረው የ22 ዓመቱ ተጫዋች፥ ከአስቸጋሪ ጅማሮ በኋላ ከእንግሊዝ እግር ኳስ አካላዊ ፈተናዎች ጋር እየተላመደ መሆኑን አረጋግጧል። ዊርትዝ በሊቨርፑል ስለነበሩት የመጀመሪያዎቹ ጥቂት ወራት ሲናገር “ቀላል ጊዜ አልነበረም” ብሏል። “ሁልጊዜ ነገሮች ወደ ላይ ብቻ ባይሄዱ ጥሩ ነው፤ ውድቀቶችን ማየት እና ከዚያ ተምሮ መጠናከር ያስፈልጋል። አሁን ላይ ጉዳዩን የማየው በዚህ መንገድ ነው፤ ይህም የበለጠ ጠንካራ አድርጎኛል። ተቃውሞዎችን ማለፍ እና መላመድ ነበረብኝ። የበለጠ ጠንካራ መሆንን እና ኳስን ጠብቆ ማቆየትን መማር ነበረብኝ” ሲል ተደምጧል።