ሩበን አሞሪም ሲሰናበቱ ዩናይትድ ስድስተኛ ደረጃ ላይ የነበረ ቢሆንም፣ በካሪክ አመራር ስር የቡድኑ አፈጻጸምና ውጤት ተሻሽሎ አሁን ላይ ሁለት ጨዋታዎች እየቀሩት ሊቨርፑልን በስድስት ነጥቦች በልጦ በሦስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ካሪክ አርብ ዕለት በሰጡት አስተያየት ስለ ወደፊት ቆይታቸው “በቅርቡ” ግልጽ እንደሚሆን አምነዋል። ያስመዘገቡት ስኬት በዋና ሥራ አስፈፃሚው ኦማር ቤራዳ እና በክለቡ የእግር ኳስ ዳይሬክተር ጄሰን ዊልኮክስ ዘንድ እውቅናን ያገኘ ሲሆን፣ ሁለቱም ኃላፊዎች ካሪክ በቋሚነት እንዲቀጥል ይፈልጋሉ። ካሪክ በፈገግታ ታጅበው “ሁለት ጨዋታዎች ይቀሩናል፤ ከዚያ ውጭ ብዙ የሚባል ነገር የለም” ብለዋል። “ሁኔታው ለሁላችንም ግልጽ ነው። ለጨዋታው እንደምንዘጋጀው ሁሉ ማለት ነው።”
“ይህ ልዩ እና የተለየ የእግር ኳስ ክለብ ነው። እንደ ደጋፊ እና እንደ ቀድሞ ተጫዋች ተመልሼ የዚህ አካል በመሆኔ እጅግ ኩራት ይሰማኛል። እንደ አንድ ደጋፊ፣ ተመልሶ መምጣትና ክለቡን መርዳት እንዲሁም ወደፊት ማራመድ አስፈላጊ ነበር። ትልቅ እርምጃ መራመድና ወደ ቻምፒዮንስ ሊግ መመለስ ጥሩ ነው፤ እስካሁን በሰራነው ስራም ደስተኞች ነን” ሲሉ ካሪክ ገልጸዋል።
ውሉ ይፈረምም አይፈረም ካሪክ ከእሁዱ ጨዋታ በኋላ ለደጋፊዎቹ ንግግር ያደርጋሉ። “ያ ለማንኛውም አስፈላጊ ነው – ደጋፊዎች የዚህ ክለብ ትልቅ አካል ናቸው” ብለዋል ካሪክ። “ስለ ወቅቱ እና ስለ ሰጡን ድጋፍ፣ በተለይም ላለፉት አራት ወራት ለኔ ላሳዩኝ ድጋፍ እናመሰግናቸዋለን። ያሳለፍነው ነገር እና ያ የተፈጠረው ትስስር ትልቅ ትርጉም አለው። ተጫዋቾቹም ያንን ተረድተዋል።” ካሴሚሮ በሰንደርላንድ ጨዋታ ላይ እንዳይሰለፍ ካደረገው ጉዳት አገግሞ በኦልድ ትራፎርድ የመሰናበቻ ጨዋታውን ለማድረግ ዝግጁ ሆኗል። ካሪክ ስለ ተጫዋቹ ሲናገሩ፡ “እዚህ ከመጣሁና ካገኘሁት በኋላ አብረን ስንሰራ ለኛም ሆነ ለኔ በግል ድንቅ ነበር፤ የሰጠን ነገር በጣም ትልቅ ነው… ባለፉት ዓመታት ውጣ ውረዶች ነበሩበት፤ ነገር ግን በዚህ መልኩ በጠንካራ ሁኔታ መጨረሱ እና ከደጋፊዎች ጋር ያለው ትስስር ማየት በጣም ደስ የሚል ነው” ብለዋል።